
ኢትዮጵያ እጣ ፈንታዋና መፃዒ እድሏ ከዓባይና ከቀይ ባህር ጋር በእጅጉ የተቆራኘ ነው – ፕሬዚዳንት ታዬ
ኢትዮጵያ ከዓባይና ከቀይ ባህር መካከል የምትገኝ ሀገር ነች፤ እጣ ፈንታዋና መፃዒ እድሏም ከሁለቱ ውሃዎች ጋር በእጅጉ የተቆራኘ ነው አሉ ፕሬዚዳንት ታዬ አጽቀ ሥላሴ።
ፕሬዚዳንቱ ይህንን ያሉት የሕዝብ ተወካዮች እና የፌዴሬሽን ም/ቤቶች 5ኛ ዓመት የሥራ ዘመን መክፈቻ ሥነ ሥርዓት ላይ ባቀረቡት የመንግሥት ዓመታዊ ዕቅድ ነው።
በዚህም ኢትዮጵያ ፍትህን ባልተከተለ መንገድና ሕዝብን ባላማከለና ባላሳተፈ አግባብ ተገልላ መቆየቷን ተናግረዋል።
ኢትዮጵያ ወደነዚህ ውሃዎች እንድትመለስና ፍትሃዊ የልማት ተጠቃሚ እንድትሆን መንግሥት በመሥራት ላይ ይገኛል ነው ያሉት።
ከሦስት አስርት ዓመታት በኋላ የባሕር በር ጉዳይን ዓለም አቀፍ የመነጋገሪያ ሐሳብ ማድረግ ተችሏል ያሉት ፕሬዚዳንቱ÷ በቀጣይነት የቀጣናችንን የጋራ የመልማት ፍላጎት ያገናዘበ ትብብርና ትስስርን ለማጠናከር ዲፕሎማሲያዊና ሰላማዊ ጥረቶች ይደረጋሉ ብለዋል።
መንግሥት ፍትሃዊና አስተማማኝ የባሕር በር ለማግኘት ከቀጣናው ሀገራት ጋር በዲፕሎማሲያዊና በሰላማዊ መንገድ ይሰራል ሲሉም ገልጸዋል።
