በርካታ የአፍሪካ ሀገራት ከኢትዮጵያ አየር መንገድ ጋር በጋራ የመስራት ፍላጎት እያሳዩ ነው – አቶ መስፍን ጣሰው

Spread the love

በርካታ የአፍሪካ ሀገራት ከኢትዮጵያ አየር መንገድ ጋር በአየር ትራንስፖርት ዘርፍ በጋራ የመስራት ፍላጎት እያሳዩ መሆኑን የኢትዮያ አየር መንገድ ግሩፕ ዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ መስፍን ጣሰው ገለጹ።

አየር መንገዱ በየጊዜው ዓለም አቀፍ አድማሱን በማስፋት ላይ መሆኑንም ተናግረዋል።

የአፍሪካ አህጉርን ደግሞ በአየር ትራንስፖርት የማስተሳሰር ተግባሩን አጠናክሮ ቀጥሏል ነው ያሉት፡፡

በአሁኑ ወቅትም በርካታ የአፍሪካ ሀገራት በአየር ትራንስፖርት ዘርፍ ከአየር መንገዱ ጋር በጋራ ለመስራት ፍላጎቶች እያሳዩ መሆኑን ገልጸዋል።

በቅርቡ የናይጄሪያ የአቪዬሽንና የኤሮስፔስ ልማት ሚኒስትር አየር መንገዱን መጎብኘታቸውንና የኢትዮጵያ አየር መንገድ ወደ ናይጄሪያ የሚያደርጋቸውን በረራዎች ማሳደግ በሚያስችሉ ጉዳዮች ላይ መወያየታቸውን ተናግረዋል።

ይህም ለአየር መንገዱም ሆነ ለናይጄሪያውያን መልካም አጋጣሚ የሚፈጥር መሆኑ ነው ዋና ስራ አስፈጻሚው የገለጹት።

በቀጣይም የኢትዮጵያ አየር መንገድ የአፍሪካ አህጉርን በአየር ትራንስፖርት ለማስተሳሰር የጀመረውን ስራ አጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል።

በ38ኛው የአፍሪካ ህብረት የመሪዎች ጉባኤ ለመታደም አዲስ አበባ የመጡ የተለያዩ የአፍሪካ ሀገራት መሪዎችና ከፍተኛ ኃላፊዎች ከኢትዮጵያ አየር መንገድ ጋር በጋራ መስራት የሚያስችሉ ፍሬያማ ውይይቶች መድረጋቸውንም አውስተዋል።

በዚህም ሀገራቱ አየር መንገዶቻቸውን ለማሳደግና አየር መንገድ የሌላቸው ሀገራት ደግሞ ማቋቋም በሚቻልባቸው ሂደቶች ላይ ውይይቶች መደረጋቸውን ገልጸዋል።

የኢትዮያ አየር መንገድ በአሁኑ ወቅት በአህጉሪቱ ከ66 በላይ ከተሞች ይበራል።

ይህም የቱሪዝም፣ የንግድ፣ የሰዎች እንቅስቃሴን በማሳለጥ፣ በምጣኔ ሃብት፣ በማህበራዊና በዲፕሎማሲ መስክ የሀገራቱን ትብብርና ተጠቃሚነት በማሳደግ ጉልህ ሚና እየተጫወተ ይገኛል ሲል ኢዜአ ዘግቧል።

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *