በሚዛን አማን ከተማ በህገ-ወጥ መንገድ ሲዘዋወር የነበረ 5,000 ሊትር ናፍጣ በቁጥጥር ስር ዋለ

Spread the love

​ በሚዛን አማን ከተማ አስተዳደር በህገ-ወጥ መንገድ ሲዘዋወር የነበረ 5,000 ሊትር ናፍጣ በቁጥጥር ስር ማድረጉን የከተማው ፖሊስ አስታወቀ።

በከተማዋ ውስጥ የሚታየውን ህገ-ወጥ የነዳጅ ዝውውር ለመግታት የሚደረገው የተቀናጀ እርምጃ ተጠናክሮ መቀጠሉ ተገልጿል።

​የሚዛን አማን ከተማ አስተዳደር ሰላምና ጸጥታ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ አስማረ ቶቲ እንደገለጹት፤ ከፖሊስና ከሌሎች የጸጥታ አካላት ጋር በመቀናጀት ህገ-ወጥ የነዳጅ ዝውውርን ለመቆጣጠር የተጀመረው ስራ ውጤት እያመጣ ይገኛል።

በተለይም በምሽት ጭምር የሚንቀሳቀስ የጋራ ግብረ-ኃይል ተቋቁሞ ኦፕሬሽን በመጀመሩ፣ ተከታታይነት ያለው ህገ-ወጥ ናፍጣና ሌሎች የነዳጅ ውጤቶች በቁጥጥር ስር እየዋሉ መሆኑን አረጋግጠዋል።

​ኃላፊው አክለውም፣ ማደያዎች የሚያስመጡት ነዳጅ በአግባቡ ለህዝብ እንዲሰራጭ ጥረት እየተደረገ ቢሆንም፣ አሁንም የችግሩ ምንጭ ሙሉ በሙሉ አለመድረቁንና በተደራጀ መልኩ በዚህ ህገ-ወጥ ተግባር ላይ የተሰማሩ አካላት መኖራቸውን ጠቁመዋል።

​የሚዛን አማን ከተማ አስተዳደር ፖሊስ አዛዥ ኮማንደር ምናሉ ታደሰ ስለ ኦፕሬሽኑ ዝርዝር መረጃ ሲሰጡ እንደገለጹት የተያዘው ነዳጅ 5,000 ሊትር ናፍጣ መሆኑን ተናግረዋል።

ናፍጣው ​በአይሱዙ ተሽከርካሪ ተጭኖ በምሽት 4:00 ሰዓት አካባቢ በፖሊስ ድንገተኛ ፍተሻ ተይዟል።

ነዳጁን ሲያጓጉዙ የነበሩ አሽከርካሪውና ረዳቱ ከነኤግዚቢቱ በቁጥጥር ስር ውለው ምርመራ እየተጣራባቸው ይገኛል።

​ኮማንደር ምናሉ አክለው እንደገለጹት፣ በትናንትናው ዕለትም ከ470 ሊትር በላይ ቤንዚንና ናፍጣ በቁጥጥር ስር መዋሉን አስታውሰዋል።

​ከቀጥታ የነዳጅ መያዝ ኦፕሬሽኑ ጎን ለጎን፣ በትራንስፖርት ዘርፉ ላይ የሚታዩ ህገ-ወጥ አሰራሮችን ለመቀነስ ተጨማሪ የነዳጅ ታንከር (ሳልቫቲ) ከተገቢው በላይ ነዳጅ ለመቅዳትና ለመነገድ ተብሎ በተሽከርካሪዎች ላይ የተገጠሙ ተጨማሪ የነዳጅ ታንከሮች (ሳልቫቲዎች) እንዲወርዱ ተደርጓል፣ ነዳጅን በየቤታቸው ደብቀው በሚሸጡ ግለሰቦች ላይ ክትትል እየተደረገ ይገኛል።

​የማደያዎች ቁጥጥርን በተመለከተ በነዳጅ ማደያዎች ላይም ተገቢው ማጣራት እየተደረገ ሲሆን፣ ግድፈት በተገኘባቸው ላይ እርምጃ መውሰድ ተጀምሯል።

​በመጨረሻም፣ ህብረተሰቡ ህገ-ወጥነትን በመከላከል ረገድ እያደረገ ያለውን ድጋፍ አጠናክሮ እንዲቀጥልና ከፖሊስ ጎን እንዲቆም የከተማው የጸጥታ አመራሮች ጥሪ አቅርበዋል ሲል የከተማ አስተዳደሩ የመንግስት ኮሙኒኬሽን ዘግቧል።

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *