



የፍትህ ዘርፍ ሪፎርም መንግስት ትኩረት የሰጠው ዋነኛ የትኩረት አጀንዳ መሆኑን የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ ጉባኤ ታገሰ ጫፎ ገለጹ።
የሀገራዊ የፍርድ ቤቶችና የፍትህ ዘርፍ ትራንስፎርሜሽን የ2016 በጀት ዓመት የ9 ወራት የእቅድ አፈጻጸም ግምገማ እየተካሄደ ነው።
የመድረኩ አላማ የአፈጻጸም ሂደቱን በመመልከት የመጡ ለውጦችን እና ቀጣይ ትኩረት የሚሹ ጉዳዮች ላይ ለመምከር ያለመ መሆኑ ተገልጿል።
አፈ ጉባኤ አቶ ታገሰ ጫፎ በመድረኩ ባደረጉት የመክፈቻ ንግግር፥ የፍትህ ዘርፍና የዳኝነት አካሉን ሪፎርም ማድረግ የመንግስት ዋነኛ የትኩረት አጀንዳ መሆኑን ገልጸዋል።
የሕግ የበላይነትን ለማረጋገጥ የፍትህ አካላት ሚና ጉልህ መሆኑንም አስታውቀዋል።
ዘርፉን የበለጠ ለማጠናከር ብቃት፣ ሥነ-ምግባርና ክህሎት ባለው የሰው ኃይል ማደራጀት እንዲሁም የቴክኖሎጂ አጠቃቀምን በማሳደግ አገልግሎት አሰጣጥን ማዘመን እንደሚገባም አስገንዝበዋል።
በመድረኩ ከአፈ ጉባኤ ታገሰ ጫፎ በተጨማሪ የፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዝዳንት ቴዎድሮስ ምህረት፣ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ምክትል አፈ ጉባኤ ሎሚ በዶ፣ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግስት ዋና ተጠሪ ሚኒስትር ተስፋዬ በልጅጌ፣ የፌደራል እና የክልል ምክር ቤቶች አፈ ጉባኤዎች፣ የፌደራልና የክልል ፍርድ ቤቶች ፕሬዝዳንቶች እና የፍትህ ቢሮ ኃላፊዎች ተገኝተዋል ሲል ኢዜአ ዘግቧል።
