የተሳሳተ የፖለቲካ አመለካከት ያላቸው እና አውርቶ አደሮች ዋነኛ የኢትዮጵያ ችግሮች ናቸው፦ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)

Spread the love

ኢትዮጵያ ውስጥ ያለው የፖለቲካ ችግር ዋነኛው መንስኤ፤ የተሳሳተ የፖለቲካ አመለካከት መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ።

የዚህ ዋና ዋና ማሳያዎች ከሆኑት መካከል አንዱ ደግሞ ኢትዮጵያ ውስጥ ያለው የስንፍና ፖለቲካ የወለደው ችግር እንደሆነ ጠቅሰዋል።

የስንፍና ፖለቲካ ግጭት፣ ፀብ፣ ተቃርኖን ይወልዳል ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ፣ የአሁኖቹን ፖለቲከኞች ከድሮ ዘመን መሳፍንቶች እና መኳንንቶች ጋር አመሳስለዋቸዋል።

“የድሮ መኳንንቶች “ሳትሠራ አትብላ” የሚለውን አይቀበሉም፤ ነገር ግን አፈር ሳይነኩ ገበሬው ያረሰውን ይበላሉ። የዛሬ ዘመን ሰነፍ ፖለቲከኞችም እጃቸው አፈር እና ጭቃ እንደማይነካው፣ ገበሬው ያረሰውን እንደሚካፈሉት መኳንንቶች ናቸው” ሲሉም ገልጸዋቸዋል።

እነዚህ ፖለቲከኞች ሥራ አያውቁም፣ ሥራ አይወዱም፣ ሥራ አይሠሩም ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፥ ሰው ካልሠራ ደግሞ አልተማረም፣ መሃይም ነው ማለት ነው ብለዋል።

በሀገራችን ሥራ የማይሠሩ፣ ግብር የማይከፍሉ፣ አገልግሎት የማይሰጡ ፖለቲከኞች መብዛታቸው ፈተና መሆኑንም ነው የገለጹት።

እኛ ሀገር አርብቶ አደር፣ አርሶ አደር፣ ላብ አደር አለ፤ አሁን ደግሞ አውርቶ አደር ተጨመረበት ብለዋል ጠቅላይ ሚኒስትሩ።

አውርቶ አደሮች ዋና ሥራቸው አባልተው መብላት ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ ካላጋጩ እና ካላባሉ ስለማይበሉ ግጭት በመፍጠር ጎፈንድ ሚ ወይ መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶችን ደመወዝ ይሰበስባሉ ብለዋል።

“እነዚህ አግልግሎትን እና ሥራን የማያውቁ ሰነፍ ፖለቲከኞች እጃቸውን ታጥበው ነገር ሸርክተው መብላት ልማዳቸው አድርገውታል” በማለት ጠቅሰዋል።

የሚሠራው ሥራ ሁሉ ትክክል እንዳልሆነ እንደሚናገሩ ያወሱት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ፣ “ለእነሱ ትክክል የሆነው ኪሳቸው የሚገባው ገንዘብ ብቻ ነው” ብለዋል።

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *