
ከእነዚህም ውስጥ በግብርናው ዘርፍ በተሰራ ሪፎርም 1 ነጥብ 8 ሚሊየን ዜጎች፣ በአገልግሎት ዘርፍ 1 ነጥብ 6 ሚሊየን ዜጎች፣ በኢንዱስትሪ ወደ 680 ሺህ ገደማ ዜጎች፣ የውጭ ሀገር ሥራ ስምሪት ከግማሽ ሚሊየን በላይ ሰዎችን መላክ ተችሏል፣ በሪሞት ስራ ከ60 ሺህ በላይ ሰዎች ስራ መያዝ መቻላቸውን አብራርተዋል።
በተለይ የወጭ ስራ ስምርትና ሪሞት ስራ ላይ ዘመናዊ በሆነ መንገድ የተጀመረው ስራ ይበል የሚያሰኝ መሆኑን ገልጸው÷ ካለው ፍላጎት አንፃር አሁንም ሥራ መፍጠር እንደሚያስፈልግ ተናግረዋል።
በሌላ በኩል ሙስናን በተመለከተ በሰጡት ማብራሪያ በኢትዮጵያ ውስጥ የተቀናጀ መንግስታዊ ሌብነት አለመኖሩን አስገንዝበው÷ ለዚህም ነው እያንዳንዱ ገንዘብ በስራ ላይ እየዋለ ያለው ብለዋል።
ይሁን እንጂ ከአገልግሎት ጋር ተያይዞ ሙስና መኖሩን ያመላከቱት ዐቢይ (ዶ/ር)÷ ዋናው መፍትሔ የሲቪል ሰርቪስ ሪፎርም መሆኑን አብራርተዋል።
በዚሁም መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት አሰጣጥ ስርዓትን በስምንት ተቋማት 41 አገልግሎቶችን በማስጀመር ከተጀመረ አጭር ጊዜ ቢሆንም ዛሬ ላይ ወደ 23 ተቋማት በማሳደግ 124 አገልግሎቶች እየተሰጡ መሆናቸውን ተናግረዋል።
የመሶብ አንድ ማዕከል አገልግሎት በመስከረም መጨረሻ አካባቢ ከ17 በላይ ቦታዎች እንዲኖር እየተገነባ መሆኑን ገልጸው÷ ይህም በሁሉም ክልሎችና አዲስ አበባ ተጨማሪ እንዲኖር እየተገነባ እንደሚገኝ አስረድተዋል።
በዚህም የዲጂታል አገልግሎት እየሰፋ ሲሄድ ከአገልግሎት ጋር ተያይዞ የሚመጣው ሙስና እየቀረ እንደሚሄድ አመላክተዋል።
