ምሁራን የህዝቡ አጀንዳ አጀንዳችን ከሆነ ከመነጣጠል ፣ ከመገፋፋትና ከመበተን ይልቅ ለአንድ አላማና ለማህበረሰቡ ለውጥ በጋራ ልንሰራ ይገባል ፦ አቶ ሀብታሙ ካፍትን

Spread the love

3ኛው የቤንች ብሔር ምሁራን ማህበር ጠቅላላ ጉባኤ በሚዛን አማን ከተማ እየተካሄደ ይገኛል።

የቤንች ሸኮ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ሀብታሙ ካፍትን መድረኩን በንግግር ሲከፍቱ እንደተናገሩት አለም ለዛሬ ስልጣኔ ፣ ዘመናዊነትና ዕድገት የበቃችው በምሁራን የፈጠራ ፣ የጥበብና የምርምር ስራዎች ታግዛ ነው ብለዋል።

ዛሬ ላይ በአለማችን እጅግ ሰለጠኑ ፣ በሳይንስና ቴክሎጂ ምጡቅ ሆኑ የሚባሉት ሀገራት ከመሬት ተነስተው ሳይሆን ለትምህርት ፣ ለጥናትና ምርምርና ለፈጠራ ስራዎች በሰጡት ልዩ ትኩረትና ዜግቻቸውን የዕውቀት ባለቤት በማድረጋቸው ነው ብለዋል።

ምሁራን ለአንድ ሀገር ፣ ህዝብና ማህበረሰብ በማህበራዊ ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ መስኮች ችግር ፈቺ የጥናት ምርምር እንዲሁም ዘላቂ ተጠቃሚነት ላይ ትኩረት ሰጥተው እየሰሩ መሆኑን ገልጸዋል። በተለይም ሰላምን በማስፈን ፣ ልማት ፣ ዕድገትና ብልጽግናን ለማረጋገጥና የህዝቡን ኑሮ ለማሻሻል የሙህራን ማህበራት ሚና የጎላ ድርሻ አለው ብለዋል።

መደራጀት ፣ መተባበርና ለጋራ ሀሳብና ተጠቃሚነት መስራት ውጤታማ እንደሚያደርግ በርካታ ተሞክሮና ልምዶችን አይተናል ያሉት ዋና አስተዳዳሪው ምሁራን የሀገር ዋልታና ካስማ ፣ የጥበብ ፣ የዕውቀትና የችግር ፈቺ ምርምርና ጥናት መፍለቂያ ማዕከላት ናቸው ብለዋል።

ምሁራን የህዝቡ አጀንዳ አጀንዳችን ከሆነ ከመነጣጠል ፣ ከመገፋፋትና ከመበተን ይልቅ የጋራ አስተሳሰብ አንድነትን በመፍጠር በጋራ መስራት ያስፈልጋል ብለዋል።

የቤንች ብሔር ምሁራን ማህበር ፕሬዝዳንት አቶ ጌታሁን ተክሌ እንደተናገሩት የምሁራን ማህበሩ የብሔሩን ባህል ፣ ቋንቋ ፣ ማህበራዊ ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ተጠቃሚነትን ማጠናከርና ማስፋትን አላማ አድርጎ መመስረቱን ገልጸዋል። ባለፉት 6 አመታትም በብሔሩ የተለያዩ ጉዳዮች ላይ ትኩረት አድርጎ ውሳኔዎችን እየወሰነና እየተገበረ እዚህ መድረሱንም ገልጸዋል።

ምሁራን በሀገር ሰላም ፣ ልማት ፣ ዕድገት እና በማህበረሱ ተጠቃሚነት ላይ ጉልህ ሚና አላቸው ያሉት አቶ ጌታሁን የብሔሩ ምሁራን ንቁ ተሳታፊና ተጠቃሚ እንዲሆኑ ፣ ራሳቸውና አካባቢያቸውን ተጠቃሚ እንዲያደርጉ እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል።

የደቡብ ምዕራብ አትዮጵያ ህዝቦች ክልል ብልጽግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ኃላፊና የማህበሩ አባል አቶ ፀጋዬ ማሞ በዙም ባስተላለፉት መልዕክታቸው ሳይማር ያስተማረን ህዝብ የሰላም ፣ የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች ምሁሩ የጥናትና ምርምር ስራዎችን በመስራት ሊያግዝ ይገባል ብለዋል። በተናጠል የሚገኙ ዕውቀቶችን ማቀናጀት ፣ ማስተሳሰርና ለጋራ ጥያቄዎች የጋራ መልስ ለማግኘት መስራት ያስፈልጋል ብለዋል።

የብሔሩ ተወላጅና በስራ ምክንያት በሌላ አካባቢ የሚገኙት አቶ ማዕረጉ ሀብተማርያምም በዙም ገብተው መልዕክት አስተላልፈዋል ሲል የዞኑ መንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ጽ/ቤት ዘግቧል።

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *