


ኢትዮጵያ ከስደትና ከስደት ተመላሾች ጋር በተያያዘ እያከናወነች ያለችውን ጥረት ኔዘርላንድሽ እንደምትደግፍ የሀገሪቱ የፍትሕና ደህነነት ሚኒስቴር የዓለም አቀፍ ጉዳዮች ዳይሬክተር ሮብ ቫን ባህሆቨን ገለጹ።
የኢሚግሬሽን እና ዜግነት አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር ወ/ሮ ሰላማዊት ዳዊት በዋና ዳይሬክተሩ ከተመራ ልዑክ ጋር ተወያይተዋል፡፡
ዋና ዳይሬክተሯ በዚህ ወቅትም ኢትዮጵያ ስደትና ከስደት ተመላሾች ጋር በተያያዘ እያከናወነች ያለችውን ተግባር በሚመለከትና በቀጣይ ከኔዘርላንድስ ጋር በዘርፉ ያለን ትብብር ይበልጥ ማጠናከር በሚቻልበት ሁኔታ ላይ ለልዑኩ ገለፃ አድርገዋል።
በተጨማሪም ተቋሙ በሪፎርም ሒደት ላይ መሆኑን እና የሚሰጡ አገልግሎቶችን በዘመናዊ ቴክኖሎጂ ለማደራጀት በርካታ ስራዎች እየተሰሩ መሆኑን አብራርተዋል፡፡
ሮብ ቫን በበኩላቸው÷ ኢትዮጵያ ስደትና ከስደት ተመላሾችን በሚመለከት እያከናወነች ያለችውን ስራ እንደሚያደንቁ ገልፀው፥ሀገራቸው በዚህ ረገድ ኢትዮጵያን ለመደገፍ ዝግጁ መሆኗን አረጋግጠዋል።
ሁለቱ አካላት በተለይም በአቅም ግንባታ ዘርፍ ላይ ተቋሙ የሚሰጣቸውን አገልግሎቶች ይበልጥ ቀልጣፋ ከማድረግ አኳያ በጋራ ሊሰሩ በሚገቡ ጉዳዮች ላይ ውይይት ማድረጋቸውን የአገልግሎቱ መረጃ ያመላክታል ሲል ኤፍኤም ሲ ዘግቧል፡፡
