



መንግሥት የሀገሪቱን የጤና ሥርዓት በማዘመንና ለዘርፉ ልዩ ትኩረት በመስጠት ተግባራዊ ሥራዎችን እያከናወነ መሆኑን የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ ጉባዔ ታገሰ ጫፎ ገለጹ።
ኢትዮጵያ ወረርሽኞችን የምትመክትበት አዲስ አቅም ገንብታለች ያሉት አፈ ጉባዔው፤ የጤና ሥርዓታችን ከመቼውም ጊዜ በላይ እየዘመነ ነው ብለዋል፡፡
አፈ ጉባዔው ይህንን ያሉት የማርበርግ ቫይረስ ወረርሽኝ ከኢትዮጵያ መጥፋቱን ተከትሎ ዛሬ በተዘጋጀው የማብሰሪያ መርሐ-ግብር ላይ ተገኝተው ባደረጉት ንግግር ነው።
ባስተላለፉት መልዕክትም፣ መንግሥት ወረርሽኝን ለመከላከልና የጤና ሥርዓቱን ይበልጥ ለማዘመን ከመቼውም ጊዜ በላይ በትኩረት እየሠራ መሆኑን አብራርተዋል። በተለይም መሰል ወረርሽኞችን ለመከታተልና ለመቆጣጠር የሚደረገው ድጋፍ ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም አረጋግጠዋል።
የኮቪድ-19 ወረርሽኝን ጨምሮ ባለፉት ጊዜያት የተከሰቱ የጤና ስጋቶችን ለመከላከል የተደረጉ ጥረቶች አበረታች ውጤት ማስመዝገባቸውን አፈ ጉባዔው አስታውሰዋል።
የማርበርግ ቫይረስ ወረርሽኝን በአጭር ጊዜ ውስጥ ለመቆጣጠርና ለመግታት በተደረገው ርብርብ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ላበረከቱ አካላትም ምስጋናቸውን አቅርበዋል ሲል ኢቢሲ ዘግቧል።
