




የክልሉ የፍትህ ቢሮ የ6 ወር ስራ አፈፃፀምና የ5 አመት ስትራቴጂ ዕቅድ ግምገማ መድረክ በቦንጋ ከተማ እየተካሄደ ነው።
የምክክር መድረኩን በንግግር የከፈቱት የክልሉ ምክር ቤት አፈ_ጉባኤ የተከበሩ አቶ ወንድሙ ኩርታ መንግስት የዜጎችን የፍትህ የማግኘት መብት በአግባቡ ተደራሽ ለማድረግ ከፍተኛ ትኩረት ሰጥቶ ከሚሰራባቸው ዘርፎች አንዱ መሆኑን ገልፀው በክልሉ የፍትህ ተደራሽነትና ውጤታማነት እያደገ መምጣቱን ገልፀዋል።
በክልሉ በተለይ የባህላዊ ፍርድ ቤቶች አደረጃጀት በአዋጅ ፀድቆ ተግባራዊ መሆን መጀመሩ የፍትሐዊነት የተደራሽነት ችግሮችን በእጅጉ መቀነሱን ገልፀዋል።
ተቋም ከመትከልና ከቅንጅት ጋር ተያይዞ የሚገጥሙ ውስንነቶች በማረም አሁንም ለፍትህ ተደራሽነትና ውጤታማነት መትጋት ይገባል ብለዋል።
የክልሉ ፍትህ ቢሮ ኃላፊ ወይዘሮ ቤቴልሄም ዳንኤል በበኩላቸው የክልሉ ፍትህ ቢሮ፤የህግ የበላይነትን ማረጋገጥና የወንጀል ህጎችን ማስከበር ላይ በሰራው ስራ ውጤቶች መመዝገባቸውን ገልፀዋል።
በ2018 በስድስት ወራት ውስጥ በሁሉም የወንጀል ምርመራ መዝገቦች የማጣራት ምጣኔ 93.5% ማድረስ እንደተቻለ ገልፀው የማስቀጣት ውሳኔውም ወደ 94% ማድረስ ተችሏል ብለዋል።
የወንጀል አቃቤ ህጎችን አቅም ማሳደግ ትኩረት ተሰጥቶት እየተሰራ መሆኑን ገልፀው በዚህም በበጀት ዓመቱ ለ275 አቃቤ ህጎች የአቅም ማጎልበቻ ስልጠና ተሰጥቷል ብለዋል።
7ኛው ጠቅላላ ምርጫ ነጻ፣ ፍትሃዊና ተዓማኒ እንዲሆን በየደረጃው ያሉ የፍትህ ተቋማት ሚናቸውን በአግባቡ እንድወጡም ጠይቀዋል።
በመድረኩ የክልሉ ከፍተኛ አመራሮችና የፍትህ ዘርፍ ባለድርሻ አካላት እየተሳተፉ ይገኛሉ።
በንጉሴ ወልደየስ
