ኢትዮጵያና እስራኤል ያላቸውን የንግድና ኢንቨስትመንት ግንኙነት የበለጠ ማጠናከር ይገባል – አፈ ጉባኤ አገኘሁ ተሻገር

Spread the love

ኢትዮጵያና እስራኤል በንግድና ኢንቨስትመንት ያላቸውን ግንኙነት የበለጠ ለማጠናከር መስራት እንደሚገባ የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ-ጉባኤ አገኘሁ ተሻገር ገለጹ።

አፈ ጉባኤ አገኘሁ ተሻገር በኡዝቤኪስታን እየተካሄደ ከሚገኘው 150ኛው የኢንተር ፓርላሜንታሪ ኅብረት/አይፒዩ/ መድረክ ጎን ለጎን በሁለትዮሽ ግንኙነት ዙሪያ ከእስራኤል የፓርላማ ቡድን አባላት ጋር ተወያይተዋል።

አቶ አገኘሁ ኢትዮጵያና እስራኤል ዘመናትን የተሻገረ መልካም ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት እንዳላቸው ጠቅሰው በንግድ፣ በኢንቨስትመንትና በቱሪዝም መስክ ያላቸውን ግንኙነት አጠናክረው መቀጠል እንዳለባቸው ገልጸዋል።

የኢትዮጵያ መንግሥት በሳይንስ፣ በቴክኖሎጂና በዘመናዊ ግብርና ዘርፎች ያለውን አሠራር አጠናክሮ መቀጠል እንደሚፈልግ ጠቅሰው በዘርፎቹ በትብብር መሥራት ሁለቱን ሀገራት ይበልጥ ውጤታማ እንደሚያደርግም አመልክተዋል።

ኢትዮጵያ ፈጣን የኢኮኖሚ እድገት እያስመዘገበች መሆኑን በመግለፅም የእስራኤል ባለሃብቶች በልዩ ልዩ ዘርፎች ቢሰማሩ ተጠቃሚ እንደሚሆኑ ተናግረዋል።

የእስራኤል ምክር ቤት አፈ ጉባኤ(Speaker of the Knesset) አሚን ኦሃና እስራኤል ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን ታሪካዊ ግንኙነት በአኮኖሚና በዲፕሎማሲ ወደ ላቀ ደረጃ የማድረስ ፍላጎት አላት ብለዋል።

የሁለትዮሽ ትብብሩን ማጠናከር እንደሚገባና የህግ አውጪ ምክር ቤቶች ትስስር ማጎልበት ወሳኝ እንደሆነ መግለጻቸውን ከምክር ቤቱ የተገኘው መረጃ ያመለክታል ሲል ኢዜአ ዘግቧል።

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *