




የኢትዮጵያ የብሪክስ ብሔራዊ የሚኒስትሮች አስተባባሪ ኮሚቴ ሁለተኛ ስብሰባውን ዛሬ ግንቦት 16 ቀን 2016 ዓ.ም አካሂዷል።
የስብሰባው ዓላማ ኢትዮጵያ በብሪክስ ስብስብ ውስጥ ያላትን ተሳትፎ መገምገም እና ቀጣይ ስራዎች ላይ አቅጣጫ ማስቀመጥ መሆኑም ተገልጿል።
የኮሚቴው ሰብሳቢና የኢትዮጵያ የብሪክስ ብሔራዊ ተወካይ አቶ ማሞ እስመለዓለም ምህረቱ፤ ኢትዮጵያ በብሪክስ እንቅስቃሴዎች ላይ የምታደርገው ንቁ እንቅስቃሴ ለኢኮኖሚያዊ እና ማህበራዊ ጥቅሞች፣ ለሀገራዊ ልማት ግቦች መሳካት እና ለባለብዙ ወገን ዲፕሎማሲ መጠናከር ያለውን ፋይዳ አብራርተዋል።
ኮሚቴው ኢትዮጵያ በተሳለጠ ሁኔታ ወደ ብሪክስ እንድትቀላቀል የሚያስችለው የኢትዮጵያ የብሪክስ ተሳትፎ ስትራቴጂ ላይም መወያየቱ ተገልጿል።
በብሪክስ ስብስብ የመግባቢያ ስምምነት እና የኢትዮጵያ ድጋፍ መግለጫ ላይም መወያየቱንም የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መረጃ ያመላክታል።
የኢትዮጵያ የብሪክስ ስብስብ አባልነት የህዝብ ለህዝብ ግንኙነት፣ኢኮኖሚያዊ እና ማህበራዊ ትብብር፣ የቴክኖሎጂ እድገት እና የሁለትዮሽ ግንኙነትን እንደሚያጠናክርም ተጠቁሟል ሲል ኢቢሲ ዘግቧል።
