
የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ከግብርና መር ወደ ብዝሃ-ዘርፍ እንዲሸጋገር የተነደፈው ፖሊሲ በእጅጉ ውጤታማ ሆኗል አሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ በ6ኛው የሕዝብ ተወካዮች ም/ቤት 5ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 2ኛ መደበኛ ስብሰባ ላይ ከምክር ቤቱ አባላት ለተነሳላቸው ጥያቄዎች በሰጡት ማብራሪያ፤ መንግስት ከሕዝብ ጋር ተሳስሮ ልማት እንዲያመጣ ግልጽ አቅጣጫ የተቀመጠው ከለውጡ ወዲህ መሆኑን ገልጸው÷ ለአብነትም መንግስትና ህዝብ ተሳስረው በአረንጓዴ ዐሻራ አማካኝነት 48 ቢሊየን ችግኞችን መትከል ችለዋል ነው ያሉት።
በዚህም ለእያንዳንዱ ችግኝ 1 ዶላር ቢወጣ በጠቅላላው 48 ቢሊየን ዶላር ለአየር ንብረት ለውጥ ኢትዮጵያ ኢንቨስት አድርጋለች ሲሉም አብራርተዋል።
2017 ዓ.ም ይቻላል ተብለው ያልታሰቡ ጉዳዮች የተከናወኑበት የስኬት ዓመት እንደነበር አንስተው÷ በአንድ ዘርፍ ላይ ተንተርሶ መስራት ከድህነት አረንቋ ስለማያወጣን ብዝኃ ዘርፍን በመከተላችን ውጤት አምጥተናል ብለዋል።
ግብርና፣ ኢንዱስትሪ፣ ማዕድን፣ ቱሪዝም እና ቴክኖሎጂ ሴክተሮች ብዝኃ ዘርፍ ሆነው ቢመሩ የኢትዮጵያን ኢኮኖሚ ሊያሻሽሉ ይችላሉ የሚል እምነት ነበረን ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ÷ ኢኮኖሚው ስር ነቀል ውጤት እንዲያመጣ በብዝኃ ዘርፍ መንግስት ከአጋር ድርጅቶች ጋር ተሳስሮ የኢትዮጵያን ዕድገት ለማፋጠን እንደሚሰራ አመላክተዋል።
