

ተቋሙ ለአገልግሎት ያበቃው አዲሱ መተግበሪያ በቴሌብር ሱፐር አፕ ውስጥ የተካተተ ሲሆን በዋናነት ግብይት፣ ማህበራዊ ግንኙነትና መረጃ ልውውጥን በአንድ መተግበሪያ የያዘ ነው፡፡
አገልግሎቱን በይፋ ያስጀመሩት የኢትዮ ቴሌኮም ዋና ስራ አስፈጻሚ ወ/ት ፍሬህይወት ታምሩ አዳዲሶቹ አገልግሎቶች የዲጂታል ህይወትን ከማቅለል ባለፈ እንደሀገር የተያዘውን የዲጂታል ገንዘብ ልውውጥ አንድ እርምጃ ወደፊት ያራምዳል ብለዋል፡፡
“ቴሌ ብር ኢንጌጅ” ደንበኞች እርስ በእርስ ወይም በግሩፕ በመሆን የጽሁፍ፣ የድምጽ፣ የምስል መልዕክት መለዋወጥና ፎቶዎችንና ተንቀሳቃሽ ምሰሎችን ማጋራት የሚያስችላቸው ሲሆን ከዚህ በተጨማሪ በገጹ ላይ ክፍያዎችን መፈጸም፣ ክፍያ መጠየቅ ክፍያን መጋራትና ሌሎች አዳዲስ አገልግሎቶችን ለመፈጸም ያስችላል፡፡
ከዚህ በተጨማሪ ከቴሌ ብር ጋር የሚሰሩ አጋሮችና ስታርት አፖችን በቀላሉ ከ44 ሚሊዮን በላይ ከሚሆኑ የቴሌብር ደንበኞች ጋር መገናኘት ያስችላቸዋል ተብሏል፡፡
ደንበኞች ያለምንም ክፍያ እንዲጠቀሙበት የተዘጋጀው “ቴሌብር ኢንጌጅ” የቀደመውን ቴሌብር ሱፐር አፕ መተግበሪያን በማሳደግ ወይም (አፕዴት በማድረግ) ማግኘትና መጠቀም አንደሚቻልም ተገልጿል፡፡
ኢቢሲ
