





የኢትዮጵያ የሐይማኖት ተቋማት ጉባኤ በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል በፀረ -ኤች አይቪ/ኤዲስ መድኃኒት ቁርጠኝነትና ታካሚዎች ህክምናቸውን በመውሰድ በቀጣይነት የማቆየት ላይ የሚመክር ክልላዊ የአድቮኬሲ መድረክ በሚዛን አማን ከተማ አካሂዷል።
በመድረኩ “መመርመር ራስን ለማወቅ፤ ቅዱሳት መጸሕፍት የፀረ – ዠኤች አይቪ/መድኃኒት መውሰድን ይፈቅዳሉ” በሚል መሪ ቃል የተካሄደ ሲሆን በመድረኩም ቫይረሱ በደማቸው ያላባቸው ወገኖች የጸረ-ኤች አይቪ/ኤድስ መድኃኒትን በሐኪም ትዕዛዝ መሠረት በቋሚነት መውሰድ እንዳይችሉ እንቅፋት የሚሆንባቸውን ጉዳዮችና የመፍትሔያቸውን ከሃይማኖት ተቋማት አስተምህሮ አንፃር በመዳሰስ የጋራ ትግበራ አቅጣጫ አስቀምጠዋል።
በመድረኩ ላይ የአድቮኬሲ፣ የተግባቦትና የማህበረሰብ ንቅናቄ ዘዴዎችን በማጠናከር ማህበረሰቡ በጸረ-ኤች አይቪ/ኤዲስ እንቀስቃሴዎች ውስጥ የሚደረገውን ተሳትፎ የበለጠ ማሳደግ እንደሚገባም ተገልጿል፡፡
በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል 14,435 ሰዎች ኤች አይቪ ቫይረስ ጋር እንደሚኖሩና 789 አዲስ ሰዎች በየዓመቱ ኤች አይቪ ቫይረስ እንደሚያዙና ክልላዊ በቫይረሱ የመያዝ ምጣኔ 0.65 መሆኑን በቀረበው ሰነድ ላይ የተገለፀ ሲሆን በክልሉ 276 ሰዎች በየዓመቱ በቫይረሱ እንደሚሞቱም በመድረኩ ተብራርቷል፡፡
ለዚህም የሃይማኖት ተቋማት እና ሁሉም ባለድርሻ አካላት ለጉዳዩ ልዩ ትኩረት ሰጥተው እንዲሰሩ ማድረግ ያስፈልጋል ተብሏል፡፡
ኤች አይቪ/ኤዲስን ለመከላከል ዘመናዊና ሐይማኖታዊ ፈውስን በጥምረት መጠቀም እንደሚቻል የሐይማኖት ተቋማት ለማህበሰቡ በተገቢው ግንዛቤ የመፈጠር ስራ መስራት እንደሚጠበቅባቸውም በመድረኩ ተመልክቷል፡፡
በመድረኩ ላይ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል የሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ ምክትል ሰብሳቢ ሐጂ መሐመድ ጂብሪል አባጆብር፤ ሁሉም የሐይማኖት ተቋማት ማህበረሰቡ ተሞ መድኃኒት ከመውሰዱ አስቀድሞ እራሱን እንዲጠብቅ በየእምናቱ ቦታ መምከርና ግንዛቤ የመፍጠር ስራ መስራት አስፈላጊ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
በየተኛውም የሐይማኖት ተቋማት አስተምህሮ ለህመም መድኃኒት መውሰድ የሚመከር በመሆኑ ለኤች አይቪ/ኤዲስን ለመከላከል ሁሉንም ፈውስ መንገዶች መጠቀም ተገቢና የሚመከር መሆኑን ምክትል ሰብሳቢ ሐጂ መሐመድ ጂብሪል አባጆብር ገልጸዋል፡፡
የሃይማኖት ተቋማት ከምንም በላይ ሰዎችን በየእምነቱ አስተምሮ መሠረት በመልካም ጎዳና እንዲጓዙ መምራት መሆኑን ገልጸው በቁርዓንና በሐዲስ መጽሐፍት ላይ የተቀመጠውን ተግባራዊ በማድረግ ሁሉም ባለድርሻ አካላት የድርሻቸውን እንዲወጡ ጥሪ አስተላልፈዋል ።
በመድረኩ የተሳተፉ አካላት በበኩላቸው የትውልድ ስጋት ለሆነው ለኤች አይቪ/ኤዲስ ግልጽ በሆነ መንገድ ከማስተማርና ከመምከር አንፃር ውስንናቶች መኖራቸውን ለዚህም ተገቢ የሆነ የክትትል ና ግንዛቤ የመፍጠር ተግባር በእጅጉ ወሳኝ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
ወጣቱን ወደ አላስፈላጊ ሱስ ውስጥ እንዲገባ የሚያደርጉ በርካታ ገፊ ምክንያቶች እንዳሉና ከዚህም አንዱ ኤች አይቪ/ኤዲስ በመሆኑ ወጣቱንና መላውን ማህበረሰብ እራሱን እንዲጠብቅና የተማሙትም ከሆኑ መድኃኒቱን እንዳያቋርጥና እንዲወስድ ማስተማርና በመምከር የድርሻቸውን እንደሚወጡም ጭምር አንስተዋል፡፡
በመጨረሻም በዚሁ በሚዛን አማን በተካሄደው ክልላዊ የአድቮኬሲ መድረክ 7ቱም የክልሉ የሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ አባላት መልዕክት በማስተላለፍ መድረኩ ተጠናቋል፡፡
በመድረኩ ክልሉ የሐይማኖት ተቋማት ጉባኤ ምክትል ሰብሳቢ ሐጂ መሐመድ ጂብሪል አባጆብር ጨምሮ የክልሉ የሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ አባላት እና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል።
በተከተል ወ/ሚካኤል
