የክልሉ የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት በኢትዮጵያና በሶማሊ ላንድ መካከል የተደረሰዉን ስምምነት አስመልክቶ በምክር ቤቱ ሰብሳቢዉ በኩል መግለጫ ሰጥቷል።
መግለጫዉን የሰጡት የክልሉ የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት ሰብሳቢ አቶ ሰለሞን አየለ በኢትዮጵያ እና በሶማሌ ላንድ መካከል የተደረሰዉ ስምምነት ሁሉን አቀፍ የትብብርና አጋርነት የሚያጠናክር በማኅበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ ፣ ፖለቲካዊና ወታደራዊ መስኮች እጅግ በጣም ጠቃሚ የሆነ ስምምነት እንደሆነ ገልጸዋል።
ጋራ ምክር ቤቱ ሰብሳቢ አቶ ሰለሞን አየለ በሰጡት መግለጫ ስምምነቱም ኢትዮጵያ የወታደራዊ ቤዝና ኮሜርሻል ማሪታይም አገልግሎት በሰጥቶ መቀበልና በኪራይ ለማግኘት የሚያስችላት በመሆኑ የክልላችን የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት የሚደግፈዉ ጉዳይ እንደሆነ ገልጸዋል።
ህም የመጀመሪያችን ሳይሆን ከዚህ ቀደምም በሀገራችንና በሶማሌላንድ መካከል ቆየት ያለ የትብብር ስምምነትም እንደነበረን የሚታወስ ነው ብለዋል አቶ ሰለሞን። የስምምነት ሰነዱም የሁለቱንም ወገኖች ታሪካዊ የሚባሉ ጥያቄዎችን የሚመልስ፣ ዝርዝር ፣ግልጽና ስትራቴጂክ አጋርነትን በዘላቂነት ለመገንባት የሚያስችል እንደሆነም ይታመናል ስሉም ሰብሰቢዉ አክለዋል።
የስምምነት ሰነዱም ጎረቤቶቻችንን በማስቀደም ላይ የተመሰረተ፤ከኢኮኖሚያዊ ፋይዳው ባሻገር ህልውናችንንና ሀገራዊ ጥቅሞቻችንን በአስተማማኝ በመጠበቅና ወደ ትልማችን በፍጥነት ለመሄድ የሚያስችል ዕድልም ይፈጥራልናል ብሎ መውሰድ እንደሚቻልም የምክር ቤቱ ሰብሳቢ አቶ ሰለሞን አየለ ገልጸዋል።
ሀገራችንም በታሪኳ የባሕር በር ባለቤት የነበረችና በተለያዩ ምክንያቶች ያጣች ይህም የታሪክ ስብራትና የትውልድ ቁጭት ፈጥሮ ያለፈ ነበር ያሉት አቶ ሰለሞን ስምምነቱ የሁለቱንም ሀገራት የላቀ ተጠቃሚነትን በሚያረጋግጥ እንደሆነ አመላክተዋል። ሀገራችን የህዝቦቿን ክብር በሚመጥን ልክ በየትኛውም ደረጃ ተገቢ ሥፍራዋን ስታገኝ ሚናዋንም ስትጫወት ብቻ እኛም እንደፖለቲካ ፓርቲዎችና የጋራ ምክር ቤት እንደሚሳካልን በማመን ልዩነቶቻችንን ከመቼውም ጊዜ በላይ በማጥበብ ተያይዘን ከፍ እንል ዘንድ ይህን አጋጣሚ እንድንጠቀምበት የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤቱ ጥሪውን ያቀርባል ብለዋል ሰብሳቢዉ።
በጋራ ከተባበርን፤ከተደጋገፍንና በጋራ ጉዳዮች ላይ በትብብር ከቆምን ድርብርብ ድሎችን እያስመዘገብን የኢትዮጵያችን ከፍታ ለማፅናት በአንድነት አብረን እንትጋ ስሉ የጋራ ምክር ቤቱ ሰብሳቢ አቶ ሰለሞን አየለ ጥሪያቸዉን አቅርበዋል።
