




”ትውልድን በስነ-ምግባር፤ ተቋምን በአሰራር” በሚል መሪ ቃል 22ኛ ዓለምአቀፍ የፀረ-ሙስና ቀን ክልላዊ ማጠቃለያ መርሐግብር በሚዛን አማን ከተማ እየተካሄደ ይገኛል።
በመድረኩ የተገኙት የክልሉ ፐብሊክ ሰርቪስና ሰው ሀብት ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ ንጉሴ ወ/ጊዮርጊስ ሙስና ለሀገር ዕድገት ማነቆ በመሆኑ ሙስናና ብልሹ አሰራርን መታገል እንደሚገባ ተናግረዋል።
በክልሉ ህብረተሰቡ ባሳተፈ ትግል ሙስናን የመከላከል አቅም ማሳደግ መቻሉን ጠቁመው በሙስናና ብልሹ አሰራር የተገኙ ሀብት የማስመሰል ስራም መሰራቱን ገልጸዋል።
ሙስናን በዘላቂነት ለመታገል በአሰራር ብቻ የሚመራ ጠንካራ ተቋም መገንባትና በስነምግባር የታነፀ ትውል መፍጠር ላይ ትኩረት ተደርጎ የሚሰራ መሆኑንም አቶ ንጉሴ ተናግረዋል።
የክልሉ ስነ-ምግባር ፀረ-ሙስና ኮሚሽን ኮሚሽነር አቶ ሙሉሸሰው ዘውዴ በበኩላቸው በክልሉ ሙስናን ለመከላከል ከባለድርሻ አካላት ጋር ዘርፈ ብዙ ተግባራት እየተከናወኑ መሆናቸውን ጠቁመዋል።
የሙስና መከላከል ስራ በአንድ ጀምበር የሚከናወን ባለመሆኑ ደካማና ለብልሹ አሰራር የተጋለጡ አሰራሮችን ማስወገድ እንደሚገባ ተናግረዋል።
ሙስና ለሀገር እድገት እንቅፋት በመሆኑ በትውልድ ግንባታ ላይ በቁርጠኝነት በመስራት የሙስናን አስተሳሰብ ከስሩ ማጥፋት እንደሚገባም ተናግረዋል።
በዓሉ በድራማ፤ በጥያቄና መልስ ውድድርና ሙስናን መታገል በሚያስችሉ ኩነቶች እየተከበረ ይገኛል።
በማጠቃለያው መርሐግብር የክልል፤ የዞንና የወረዳ የስራ ኃላፊዎች፤ በዘርፉ የሚያገለግሉ መንግስት ሰራተኞችና ባለድርሻ አካላት እየተሳተፉ ይገኛሉ ሲል የደቡብ ምዕራብ ሚዲያ ኔትወርክ ዘግቧል።
