



የግብርና ሚኒስትር ዶክተር ግርማ አመንቴ ከዓለም ባንክ ዋና ዳይሬክተር ዶክተር ፍሎሪበርት ንጋሩኮ ጋር ተወያይተዋል፡፡
ሚኒስትሩ መንግስት ባለፉት 5 ዓመታት ለግብርናው ዘርፍ ትልቅ ትኩረት በመስጠት ዘርፈ ብዙ ስራዎችን በማከናወን ላይ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
በዓለም ባንክ የበጀት ድጋፍ ህብረተሰቡን ተጠቃሚ የሚያደርጉ የተለያዩ ፕሮጀክቶች በመተግበር ላይ መሆናቸውን ገልጸው፤ ባንኩ ኢትዮጵያ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የምታደርገውን ጥረት ይበልጥ እንዲያግዝ ጠይቀዋል፡፡
ዶክተር ግርማ አመንቴ የግብርናውን ዘርፍ ከዝናብ ጥገኝነት ለማላቀቅ፣ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ፣ የኤክስፖርት ምርትን በስፋት እና በጥራት ለማምረት እንዲሁም ከውጭ የሚገቡ የግብርና ምርቶችን በሀገር ውስጥ ለመተካት እየተሰሩ ያሉ ስራዎችን ለዳይሬክተሩ አብራርተዋል፡፡
የዓለም ባንክ ዋና ዳይሬክተር በበኩላቸው ኢትዮጵያ የግብርናውን ዘርፍ ለማዘመን እና የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የምታደርገውን ጥረት ባንኩ እንደሚደግፍ መናገራቸውን የግብር ሚንስቴር መረጃ ያመላክታል ሲል ኢዜአ ዘግቧል፡፡
