የኮንስትራክሽን ዘርፉን ለማዘመን በትኩረት እየተሰራ ነው – ወ/ሮ ጫልቱ ሳኒ

Spread the love

የኮንስትራክሽን ዘርፉን ይበልጥ ለማሳደግና ለማዘመን በትኩረት እየተሰራ ነው አሉ የከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስትር ወ/ሮ ጫልቱ ሳኒ፡፡

ዓለም አቀፍ የኮንስትራክሽን ኢንዱስትሪ እና የምስራቅ አፍሪካ መሰረተ ልማት ኤክስፖ በነገው ዕለት በአዲስ አበባ ሚሊኒየም አዳራሽ መካሄድ ይጀምራል፡፡

ወ/ሮ ጫልቱ ሳኒ እንዳሉት÷ ኮንስትራክሽን የአንድ ሀገር እድገት በትክክለኛ መንገድ ላይ እንደሚገኝና ኢኮኖሚው እያደገ መምጣቱን የሚያመላክት ነው፡፡

ዘርፉ ለኢትዮጵያ አጠቃላይ የሀገር ውስጥ ጠቅላላ ምርት 19 በመቶ እያበረከተ መሆኑን ጠቅሰው÷ አሁን ላይ ከፍተኛ መነቃቃት እየታየበት እንደሚገኝ አስገንዝበዋል፡፡

በኮንስትራክሽን ዘርፉ የሚስተዋሉ ችግሮችን በሒደት ለመፍታት በትብብርና በቅንጅት እንደሚሰራም ነው የተናገሩት፡፡

መሰል ዓለም አቀፍ ሁነቶች በኢትዮጵያ መካሄዳቸው ለኮንፈረንስ ቱሪዝም መጎልበት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደሚያበረክቱ አስረድተዋል፡፡

በዓለም አቀፉ የኮንስትራክሽን ኢንዱስትሪ ኤክስፖ ቻይና፣ ጀርመን፣ ሕንድ፣ ጣልያን እና የተባበሩት ዓረብ ኤሚሬቶችን ጨምሮ ከ20 በላይ ሀገራት ይሳተፋሉ፡፡

ኤክስፖው በዘርፍ የተሰማሩ አካላት አዳዲስ ፈጠራዎችንና ልምዶች እንዲቀስሙ፣ ለቴክኖሎጂ ሽግግር እንዲሁም የአሰራር ሥርዓቶችን እንዲለዋወጡ የሚያስችል ነው፡፡

127 ዓለም አቀፍ እና 39 የሀገር ውስጥ የዘርፉ ኩባንያዎች የሚሳተፉበት ኤክስፖው ከሰኔ 19 እስከ 21 ቀን 2017 ዓ.ም ይካሄዳል ሲል ኤፍኤም ሲ ዘግቧል፡፡

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *