




በዳውሮ ዞን ታርጫ ከተማ አስተዳደር ቅዱስ ዮሰፍ ካቶሊክ 1ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተገኝተው ክትባቱን ያስጀመሩት የዳውሮ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ዳዊት ገበየሁ የነገ ሀገር ተረካቢ የሆኑ ህጻናትን ጤና ለመንከባከብ መንግስት እንደ ሀገር መጠነ ሰፊ ሥራዎችን እየሰራ ይገኛል ብለዋል።
በዚሁ ሂደት ተጨባጭ ውጤቶች መመዝገባቸውንና የአገልግሎት ተደራሽነቱንም ከፍ ለማድረግ መቻሉን ዋና አስተዳዳሪው አመላክተዋል።
እንደ ዞን በእናቶችና ህጻናት ጤና ክብካቤ ላይ በየደረጃው ውጤታማ ተግባራት እየተከናወኑ እንደሚገኝ የገለጹት ዋና አስተዳዳሪው ውጤቱን አጠናክሮ ለማስቀጠል የተቀናጀ ርብርብ እየተደረገ እንደሚገኝም አብራርተዋል።
የክትባት ተደራሽነቱን ሙሉ በሙሉ ለማሳካት የሚመለከታቸው ሁሉ የተጣለባቸውን ኃላፊነት በብቃት እንዲወጡ አቶ ዳዊት አሳስበዋል።
የክልሉ ጤና ቢሮ ኃላፊ አቶ ኢብራሂም ተማም በበኩላቸው ክትባቱን ሰኬታማ ለማድረግ በክልሉ ሁሉም አካባቢዎች አስፈላጊ ግብአቶችን ተደራሽ ለማድረግ ተችሏል።
የፖሊዮ በሽታን ከአገር ለማጥፋት የሚደረገውን ጥረት ውጤታማ ለማድረግ እንደ ክልል የተቀናጀ ጥረት እየተደረገ እንደሚገኝም አቶ ኢብራሂም ጠቁመዋል።
የህጻናትን ጤና መንከባከብ በትውልድ ግንባታ ሂደት ላይ የሚኖረውን ከፍተኛ ፋይዳ በመገንዘብ መንግስት ለህጻናት የሚሰጡ የህክምና አገልግሎቶችን አጠናክሮ መቀጠሉንም ጠቁመዋል።
የፖሊዮ በሽታን ከሀገር ለማጥፋት የሚደረገው ጥረቱ የዚሁ ተግባር አካል ነው ያሉት አቶ ኢብራሂም ለዚሁ ስኬት በየደረጃው የሚገኙ የሴክተሩ አመራሮች፣ ባለሙያዎች እና ሌሎች የባለድርሻ አካላት ከፍተኛ ኃላፊነት ተጥሎባቸዋል ብለዋል።
ስለሆነም ለክትባቱ በተቀመጠው የጊዜ ገደብ ሁሉም ህጻናት የአገልግሎቱ ተጠቃማዎች እንዲሆኑ በትኩረት ይሰራል ብለዋል አቶ ኢብራሂም ።
ክትባቱ ከ5 ዓመት የዕድሜ ክልል በታች ላሉ ወደ 6 መቶ ሺህ ለሚጠጉ ህጻናት እየተሰጠ እንደሚገኝም አቶ ወሰን ገልፀዋል።
በዕለቱ በታርጫ ጠቅላላ ሆስፒታል ህጻናት እንደተወለዱ የሚሰጠው የጉበት በሽታ መከላከያ ክትባት ክልላዊ ማስጀመሪያ መርሀ ግብርም ተካሂዷል።
በታርጫ ጠቅላላ ሆስፒታል ግንባታው እየተጠናቀቀ የሚገኝ የእክስጂን ማምረቻ ጉብኝት ተካሂዷል።
ግንባታው ሲጠናቀቅ የሆስፒታሉን ተግባር ይበልጥ ከማሳለጥ ጎን ለጎን በአጎራባች አካባቢ ለሚገኙ የጤና ተቋማትም የተሻለ ዕድል እንደሚፈጠር ተመላክቷል።
