
ስምምነቱን ሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር፣ ቦንጋ ዩኒቨርሲቲ እና በሩሲያ የፓን አፍሪካ የመንግስትና የግል አጋርነት የልማት ማዕከል ናቸው የተፈራረሙት፡፡
ስምምነቱ የእናቶችንና የጨቅላ ህፃናትን ህይወት ለማሻሻል የሚረዳ በአይነቱ በኢትዮጵያ የመጀመሪያው ‘ሚድ ዋይፈሪ’ ማዕከል እንደሚሆን ተጠቅሷል፡፡
የሩሲያው የፓን አፍሪካ የመንግስትና የግል አጋርነት የልማት ማዕከል ወደ ሀገር እንዲመጣ የቦንጋ ዩኒቨርሲቲ ላበረከተው አስተዋፅኦ የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ዶክተር ኤርጎጌ ተስፋዬ አመስግነዋል፡፡
የቦንጋ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ዶክተር ጴጥሮስ ወ/ጊዮርጊስ በበኩላቸው÷ ማዕከሉ አረጋውያንን ለመደገፍ የሚያስችል አገልግሎቶችንም እንደሚያካትት ገልጸዋል።
በሩሲያው የፓን አፍሪካ የመንግስትና የግል አጋርነት የልማት ማዕከል ዋና ስራ አስፈጻሚ ኦክሳና ማያሮቫ÷ ማዕከሉ ከሩሲያ መንግስት ጋር በመተባበር ይህንን ማእከል በኢትዮጵያ ለመገንባትና በሌሎች መስኮች ላይ አብሮ እንደሚሰራ መግለጻቸውን የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር መረጃ ያመላክታል ሲል ዴሬቴድ የቦንጋ ቅርንጫፍ ዘግቧል፡፡
