በስድስት ወራት ከ20 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት በዋና ዋና ሰብሎች መሰብሰብ ተችሏል – አቶ ማስረሻ በላቸው

Spread the love

የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል የመንግስትና የፓርቲ የ2018 በጀት ዓመት የስድስት ወራት ዕቅድ አፈጻጸም ግምገማ መድረክ በመካሄድ ላይ ይገኛል።

በአፈጻጸም ግምገማው በክልሉ ግብርናን በማዘመን ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ በተሰሩ ተግባራት ላይ ማብራሪያ የሰጡት የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድርና የግብርና ቢሮ ኃላፊ አቶ ማስረሻ በላቸው፥ ከአምናው ተመሳሳይ ወቅት ጋር ስነጻጸር በምርት ዘመኑ የማሳ ሽፋንና የምርት መጠነ መጨመሩን ጠቅሰዋል።

በ2017 የበልግ እና በ2018 የመኸር ምርት በክልሉ 20.7 ሚሊዮን ኩንታል ምርት በዋና ዋና ሰብሎች መሰብሰቡን ነው አቶ ማስረሻ ያብራሩት።

ምርታማነትን ለማሳደግ የሚረዱ የግብርና ቴክኖሎጂ አጠቃቀም ከጊዜ ወደ ጊዜ መሻሻል እያሳየ ነው ያሉት አቶ ማስረሻ ያደሩ ግብዓቶችን በመጪው የበልግ እርሻ አሟጦ መጠቀም ይገባል ብለዋል።

ከተረጂነት ወደ ተሟላ ምርታማነት ለመሻገር እየተከናወነ ያለው ተግባር በክልሉ አመርቂ ውጤት እያመጣ መኾኑን የጠቆሙት አቶ ማስረሻ በሁሉም የክልሉ አከባቢ ሰብዓዊ ድጋፍ በራስ አቅም የመሸፈን የቅድመ ዝግጅት ተግባር መጠናከር አለበት ብለዋል።

የአግልግሎት አሰጣጥ በማሻሻል የዜጎችን እርካታ ለማሳደግ በተመረጡ የክልሉ ከተሞች የተጀመረውን የመሶብ አንድ ማዕከል አግልግሎት ግንባታ በተያዘው ጊዜ ለማጠናቀቅ በትኩረት እየሰሩ እንደሚገኙ ነው የዞን ዋና አስተዳዳሪዎች በመድረኩ ያነሱት።

በበጀት ዓመቱ ቀሪ ጊዜያት መደበኛ የመንግሥትና የብልጽግና ፓርቲ የንቅናቄ አጀንዳዎችን በተሻለ መልኩ ለመፈጸም በቁርጠኝነት እንደሚሰሩም ነው አስተዳደሮች የገለጹት።

በክልሉ የተጀመረው የድጋፍ ክትትል ግብረ መልስ አግባብ ችግር ፈቺ፣ ውጤታማና ምቹ አጋጣሚ በመኾኑ በቀጣይነት ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት ዋና አስተዳዳሪዎች ጠይቀዋል።

በዕድገቱ በዛብህ

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *