


በኮንታ ዞን ሼታ ጫራ ቀበሌ መጋ መንደር ላይ በቅንጅት የለማው የስንዴ ምርጥ ዘር ብዜት የክልሉ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት እየሰራ ያለው አካል መሆኑም ተገልጿል ።
በኮንታ ዞን አመያ ዙሪያ ወረዳ ሼታ ጫራ ቀበሌ መጋ መንደር በኩታ ገጠም አርሶ አደር ማሳ የለማ የስንዴ ዘር ብዜት የመስክ ምልከታ ተደርጓል ።
የክልሉ ግብርና ምርምር ኢንስትቲዩት ከኮንታ ዞን ግብርና መምሪያ ጋር በመተባበር ያከናወነው ነው።
በመስክ ምልከታው ተገኝተው ንግግር ያደረጉት የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር እና የግብርና ቢሮ ኃላፊ አቶ ማስረሻ በላቸው በክልሉ ከ328 ሺህ በላይ ሄክታር መሬት በመኸር ሰብል መሸፈኑን ተናግረዋል ።
እስካሁን ባለው መረጃ ከ286 ሺህ በላይ ሄክታር ሰብል 5.2 ሚሊየን ኩንታል ምርት እንደሚሰበሰብ ተናግረዋል ።
በክልሉ የሚስተዋለውን የምርጥ ዘር አቅርቦት ችግሮችን ለመቅረፍ የምርጥ ዘር ድርጅት በማቋቋም ወደ ተግባር መገባቱንም አቶ ማስረሻ በላቸው ተናግረዋል ።
ተባባሪ ባለድርሻ አካላትን በማስተባበር በቅንጅት በክልሉ ከ1600 ሄክታር በላይ መሬት የምርጥ ዘር ብዜት እየተከናወነ መሆኑንም አቶ ማስረሻ ተናግረዋል ።
የክልሉ ግብርና ኢንስቲትዩት ከኮንታ ዞን ጋር በመተባበር በሼታ ጮራ ቀበሌ የለማው 50 ሄክታር የስንዴ ምርጥ ዘር ብዜት ውጤታማና አስደማሚ ነው ሲሉም ተናግረዋል ።
ዳገታማና ቁልቁለታማ መልክዓምድራዊ አቀማመጥ ባለበት አካባቢ ከ150 በላይ የበሬ ሜካናይዜሽን እርሻ በተከናወነበት በዚህ ስፍራ የተገኘው ውጤት በሁሉም አካባቢዎች ተሞክሮው እንዲስፋፋ በትኩረት ይሰራልም ብለዋል።
የኮንታ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ነጋ አበራ በበኩላቸው ምርትናምርታማነትን ለማሳደግ ምርታማ የሆኑ ምርጥ ዘሮችን መጠቀም ይኖርብናል ብለዋል።

የመሬት አቀማመጡ ለትራክተር እርሻ በማይመችበት ሼታ ጫራ ቀበሌ በበሬ እርሻ ውጤታማ የስንዴ ምርጥ ዘር ብዜት ማከናወን ችለናል ብለዋል።
የክልሉ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር አቶ አማኑኤል ዓለሙ በበኩላቸው ፖሊሲን መሠረት ያደረጉ የግብርና ምርምር ስራዎች እየተሰሩ መሆኑን ተናግረዋል ።
የክልሉን የምርጥ ዘር ችግር ለመቅረፍ ኢንስቲትዩቱ 32 የምርምር ቴክኖሎጂ ጥናቶች መጠናቀቃቸውን እና 129 የሚሆኑ ደግሞ በሂደት ላይ እንደሚገኙ አቶ አማኑኤል ተናግረዋል ።
ሾሪማ የተሰኘው የስንዴ ዝርያ 43 አርሶአደሮችን በማሳተፍ በ50 ሄክታር መሬት ለምቷል።
በመስክ ምልከታው የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልላዊ መንግስት ምክትል ርዕሰ መስተዳድር እና የግብርና ቢሮ ኃላፊ አቶ ማስረሻ በላቸውና ሌሎች የክልልና የዞን የስራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል።
በታጠቅ አበበ
