







የ2016 ዓመተ ምህረት የካፋ ዞን እግር ኳስ ክለቦች ሻምፒዮና ለ11 ቀናት ሲካሄድ ቆይተው ፍጻሜ አግኝቷል።
የአንድ ሀገር ኢኮኖሚያዊ፣ማህበራዊና ፖለቲካዊ ዘርፎችን ለማጠናከር የስፖርት ዘርፍ ድርሻ ከፍተኛ መሆኑን የካፋ ዞን ባህል ቱሪዝምና ስፖርት መምሪያ ኃላፊ አቶ ነፃነት ብርሃኑ ተናግረዋል።
ዞናችን በስፖርት ዘርፍ ህዝባዊ መሠረት ይዞ እንዲሄድና የዜጎችን የስፖርት ተሳትፎ ለማረጋገጥ በተሰራው ስራ በአፍሪካ ብሎም በአለም አቀፍ ደረጃ በሩጫ፣በብስክሌትና በጅምናዝየም ዞናችንን ያስጠሩ ስፖርተኛች ማፍራት የተቻለ መሆኑን ገልጿል።
በዚህ የእግር ኳስ ክለቦች ሻምፒዮና 9 ወረዳዎች፣ 5 ከተማ አስተዳደሮች ቦንጋ ፖሊ ቴክንክ ኮሌጁን ጨምሮ 15 ክለቦች እና 3 መቶ 75 ተጫዎቾች መሳተፋቸውን የባህል ቱሪዚምና ስፖርት መምሪያው ኃላፊው አቶ ነፃነት ብርሃኑ ተናግረዋል።
በክልል ደረጃ የሚካሄደው የእግር ኳስ ክለቦች ሻምፒዮና አውራዳ ከተማ አስተዳደር፣ጊምቦ ዳዲበን፣ሺሽንዳ ከተማ አስተዳደር፣ቦንጋ ከተማ አስተዳደር ፣ዴቻ ወረዳና ጌሻ ወረዳ የእግር ኳስ ክለቦች ዞኑን ወክለው እንደሚጫወቱ ኃላፊው ገልጸዋል።
የካፋ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ተወካይና የፋይናንስና ኢኮኖሚ ልማት መምሪያ ኃላፊው አቶ መቅደስ ማሞ እንዳሉት ስፖርት ፍቅርን፣አንድነትንና ትብብርን የሚያጎላ ትልቅ ዘርፍ ነው ብለዋል።
በዞናችን የተለያዩ የስፖርት ዘርፎች ላይ አመርቂ ውጤቶች እየተመዘገቡ ነው ያሉት ኃላፊው ይህንን አጠናክሮ ማስቀመጥ እንደሚገባም አሳስቧል።
የ2016 ዓመተ ምህረት የካፋ ዞን የእግር ኳስ ክለቦች ሻምፒዮና ለመሆን ከጊምቦ ዳዲበን ጋር የተጫወቱት አውራዳ ከተማ አስተዳደር 1 ለ 0 በሆነ ውጤት አሸንፈው የዋንጫ ባለቤት ሲሆን ጊምቦ ዳዲበን 2ኛ ደረጃ በመሆን አጠናቋል።
የካፋ ዞን እግር ኳስ ክለቦች ሻምፒዮና 3ኛ ደረጃ ለመውጣት ከቦንጋ ከተማ አስተዳደር ጋር የተጫወተው የሺሽንዳ ከተማ አስተዳደር 2 ለ 1 በሆነ ውጤት አሸንፏል።
የ2016 የካፋ ዞን እግር ኳስ ክለቦች ሻምፒዮና ከተሳተፉ 15 ክለቦች ውስጥ ጨታ ወረዳ የፀባይ ዋንጫ ተሸላሚ ሆኗል።
የዘንድሮን የመላው የካፋ ዞን የእግር ኳስ ክለቦች ሻምፒዮና በተሳካ ሁኔታ እንዲካሄድ የበኩላቸውን አስተዋጽኦ ያበረከቱ ተቋማቶችን፣ ግለሰቦችና ተሳታፊ ክለቦች የምስክር ወረቀት መሰጠቱን የካፋ ዞን የመንግሥት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ጽ/ቤት መረጃ ያመለክታል።
