በአንድ ጀንበር ተከላ ከ21 ሚሊዮን በላይ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞችን ለመትከል ዝግጅት ተደርጓል።

Spread the love

በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል በ2017 ዓ/ም የአንድ ጀንበር ተከላ ክልላዊ የአረንጓዴ አሻራ መርሀግብር ከ21 ሚሊዮን በላይ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞችን ለመትከል ዝግጅት መደረጉን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ።

የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድርና የግብርና ቢሮ ሀላፊ አቶ ማስረሻ በላቸው እንደተናገሩት የ2017 ክልላዊ የአንድ ጀንበር የአረንጓዴ አሻራ መርሃ በዕለቱ ዘርፈብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ከ21 ሚሊዮን በላይ ችግኞች ለመትከል የሚያስችል ዝግጅት ተደርጓል ብለዋል።

ክልላዊ የማብሰሪያ ፕሮግራሙ በዳዉሮ ዞን ታርጫ ዙሪያ ወረዳ ጎሪቃ በርሳ ቀበሌ እንደሚከናወን የገለጹት አቶ ማስረሻ በዚህ ለተከላ በተዘጋጀው 10.7ሄ/ር ላይ ይተከላል ብለዋል።

አረንጓዴ አሻራ የአፈር መከላትን በመከላከል ለአየር ንብረት ለዉጥ የማይበገር ኢኮኖሚ በመገንባት የላቀ አስተዋጽዎ እያበረከተ እንደሚገኝ የገለጹት አቶ ማስረሻ፥ ባለፉት ስድሰት ዓመታት የአረንጓዴ አሻራ ተከላ መርሀግብር በክልሉ ከ1.3 ቢሊዮን ችግኞችን መትከል መቻሉን አብራርተዋል።

በ2017 አረንጓዴ አሻራ መርሀ ግብር እንደ ክልል 309.9 ሚሊዮን ችግኞችን በጥምር ግብርና እና ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸዉ ችግኞች ለመትከል መታቀዱን የገለጹት አቶ ማስረሻ፥ በተጨማሪነትም 88.5 ሚሊየን የቡና ችግኝ ፣ 625,555 ሻይ ችግኞች ለመትከልና፣ በጠቅላላዉም 453 ችግኞችን በማዘጋጀት 399 ሚሊየን ችግኞች የሚተከል ይሆናል ብለዋል።።

በክልሉ በ2017 በጀት ዓመት የሁለተኛ ዙር አረንጓዴ አሻራ መርሀ ገብር ቡናና ጨምሮ 275 ሚሊዮን በላይ ችግኞች በመትከል 123 ሺህ 348.4 ሄ/ር መሬት መሸፈን መቻሉንም ነው ኃላፊው የገለጹት።

በ2017 ዓ.ም የሁለተኛ ዙር አረንጓዴ አሻራ፥ የአንድ ጀንብር ተከላ ‘‘በመትከል ማንሰራራት’’ በሚል መሪ ቃል ሐምሌ 24፣ 21 ሚሊየን የደን ፣ ጥምር ደንና ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸዉ ችግኞች በ6 መቶ 54 የተከላ ሳይቶች 7924.90ሄ/ር መሬት የሚሸፈን እንደሆነም ነው አቶ ማስረሻ የጠቆሙት።

በክልሉ ሁሉም መዋቅሮች ለተከላ የሚሆኑ ችግኞችን የማዘጋጀትና የተከላ ቦታ ዝግጅት ጉድጓድ ዝግጅት የተከናወነ መሆኑን የገለጹት አቶ ማስረሻ፥ በአንድ ጀንበር ተከላዉም ወ 555 ሺህ 712 ሴ 486 ሺህ 420 ድ 1ሚሊየን 42 ሺህ 132 የህብረተሰብ ክፍሎች እንደሚሳተፉ ተናግረዋል።

በክልላዊ የማብሰሪያ ፕሮግራሙ ሁሉም የክልሉ ነዋሪ ባለበት አከባቢ በነቂስ በመውጣት የድርሻዉን እንዲወጣም አቶ ማስረሻ ጥሪ አስተላልፏል።

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *