የኢትዮጵያ የሚዲያ ልህቀት ማዕከል ስራ ጀመረ

Spread the love

የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙሃን ባለስልጣን የመገናኛ ብዙሃንን አቅም ለማሳደግ በሚል ያቋቋመው የሚዲያ ልህቀት ማዕከል በይፋ ስራ ጀምሯል።

በማስጀመሪያ መርሐ ግብሩ ላይ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ ጉባኤ ታገሰ ጫፎ እንዳሉት፤ በሰላም፣ በመልካም አስተዳደር ዘርፍም ሆነ በኢኮኖሚ ጉዳዮች ላይ ወቅታዊና ትክክኛ መረጃ በማቅረብ መገናኛ ብዙሃን ሚናቸው የጎላ ነው።

ሚዲያዎች ለማህበረሰብ እድገት የራሳቸውን ሚና በመጫወት የኢትዮጵያን እድገት ለማረጋገጥ ይድርሻቸውን መወጣት አለባቸው ብለዋል።

በኢትዮጵያ መልክ የተቋቋመው የሚዲያ ልህቀት ማዕከሉ የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅም ማስጠበቅ የሚችል ከመሆን ባለፈ የህዝብን የመረጃ ተደራሽነት ለማሳካት የጎላ ሚና እንደሚኖረው ተናግረዋል።

የጠቅላይ ሚኒስትሩ የማህበራዊ ዘርፍ አማካሪ ሚኒስትር ሙዓዘ ጥበባት ዲያቆን ዳንኤል ክብረት በበኩላቸው፤ የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙሃን ብሔራዊ ጥቅምን፣ ሕብረ ብሔራዊ አንድነትን፣ የወል ትርክትን እና የኢትዮጵያን ብልፅግና ለማረጋገጥ መስራት እንዳለባቸው አስገንዝበዋል።

መገናኛ ብዙሃኑ በእነዚህ አራት ጉዳዮች ላይ የጋራ አንድነትና መግባባት ሊኖራቸው እንደሚገባ ጠቅሰው፤ ማዕከሉ ይህንን ሊያረጋግጥ እና ሊያሳድግ የሚችል ሆኖ መምጣቱን አብራርተዋል።

ማዕከሉ የመገናኛ ብዙሃንን አቅም በመገንባት ብሔራዊ ጥቅምን ያማከለ ስራ እንዲሰሩ እና የጋራ ትርክትን በመቅረፅ ረገድ የራሳቸውን ሚና እንዲወጡ የሚደግፍ ተቋም መሆኑ ተገልጿል።

በመርሐ ግብሩ ላይ የመንግስት ኮሚኒኬሽን አገልግሎት ሚኒስትር እናትዓለም መለሰ፣ የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ተጠባባቂ ፕሬዚዳንት ሳሙኤል ክፍሌ (ዶ/ር) ጨምሮ ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል ሲል ኤፍኤም ሲ ዘግቧል።

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *